የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በክረምት እና በቅዳሜ እና እሁድ መርሀ ግብር 4,000 የቅድመ አንደኛ ደረጃ መምህራን ለቀጣይ ሶስት አመት ለማሰልጠን ከደብረ ብርሀንና አሰላ መምህራን ትምህርት ኮሌጆች ጋር የውል ስምምነት ተፈራረመ።
በመርሀ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘላለም ሙላቱ፣ምክትል ቢሮ ኃላፊዎች፣የቢሮ አማካሪዎች፣ የደብረ ብርሀን መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲን ረዳት ፕሮፌሰር መባ ፈጠነ፣የአሰላ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲን ረዳት ፕሮፌሰር ጎሳ ግርማን ጨምሮ የአዲስ አበባ መምህራን ማህበር ስራ አስፈጻሚዎች እንዲሁም ሰልጣኝ መምህራኖችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሌሎች የትምህርት ባለሙያዎች የተገኙ ሲሆን የደብረ ብርሀን መምህራን ትምህርት ኮሌጅ 2,500 መምህራንን በዲፕሎማ ለማሰልጠን እንዲሁም አሰላ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ 1,500 መምህራንን በዲፕሎማ ለማሰልጠን ውል ፈጽመዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘላለም ሙላቱ በመርሀ ግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት የመምህራንን አቅም የማጎልበትና በተለያዩ ስልጠናዎች ማብቃት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ዋነኛው ተግባር መሆኑን ገልጸው የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት የሚያስተምሩ መምህራን የትምህርት ደረጃቸውን ከሰርተፊኬት ወደ ዲፕሎማ ማሳደጋቸው በአዲሱ ስርአዓተ ትምህርት ለትምህርት እርከኑ የተቀመጠውን ስታንዳርድ ለማሟላት ከማገዙ ባሻገር በቅድመ አንደኛ ደረጃ ያለውን የመምህራን እጥረት ለመቅረፍ እንደሚረዳ አስታውቀዋል።
ኃላፊው አክለውም የትምህርት እድሉን ያገኙ ሰልጣኝ መምህራን ትምህርታቸውን በአግባቡ ተከታትለው በማጠናቀቅ ህጻናቱ ማግኘት የሚገባቸውን ዕውቀት ማስጨበጥ እንደሚጠበቅባቸው የአደራ መልዕክታቸውን ያስተላለፉ ሲሆን ኮሌጆቹም ቢሮው ያቀረበውን ጥያቄ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ተቀብለው ለመምህራኖቻችን እድሉን ስላመቻቹ ላቅ ያለ ምስጋና እንደሚገባቸው ጠቁመዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቴ ሳምሶን መለሰ በበኩላቸው የቅድመ አንደኛ ደረጃ መምህራኑ የዚህ እድል ተጠቃሚ መሆናቸው ህጻናቱ ጥራቱን የጠበቀና እድሜያቸውን ያማከለ ትምህርት እንዲያገኙ ከማስቻሉ ባሻገር ለአንደኛ ደረጃ ትምህርት ዝግጁ እንዲሆኑ እንደሚረዳቸው አስገንዝበዋል።
መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት ማሰፈንጠሪያዎቹን ይጫኑ!
You Tube: https://www.youtube.com/watch?v=TWkBGoeYCNQ…
Telegram ፡ https://t.me/wwwAddisAbabaeducationbureau
Twitter ፡ https://twitter.com/aacaebc
Face book: https://www.facebook.com/aacityeducationcommunication
Blog: – http://www.aacaebc.wordpress.com/
Website: – aaceb.gov.et
Email;- aacaebc@gmail.com
Instagram: – https://www.instagram.com/aacaeb/
ባልታጠበ እጅ አይንዎን አፍዎን እና አፍንጫዎን ባለመንካት በዙሪያዎ ላሉ ሰዎች አርአያ ይሁኑ!
