ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 በሚገኘው ሀና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች በምግብ መመረዝ ምክንያት ጉዳት እንደደረሰባቸው የሚወራው ወሬ ሀሰት መሆኑ ተገለጸ።
ጉዳዩን አስመልክቶ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘላለም ሙላቱ ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምገባ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬከተር አንቺነሽ ተስፋዬ እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶክተር ሙሉጌታ እንዳለ መግለጫ ሰጥተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘላለም ሙላቱ እንዳስታወቁት በትምህርት ቤቱ ለግዜው ባልታወቀ ምክንያት ሁለት ተማሪዎች አደጋ እንዳጋጠማቸውና እነዚህን ተማሪዎች ያዩ የተወሰኑ ልጆች በድንጋጤ ራሳቸውን በመሳታቸው ወደ ህክምና ማዕከል መወሰዳቸውን ገልጸው ተማሪዎቹ በተደረገላቸው ምርመራ ምንም አይነት ከምግብ መመረዝ ጋር የተገናኘ ችግር እንዳላጋጠማቸው በመረጋገጡ ወደ ቤታቸው እንዲሄዱ መደረጉን አስረድተዋል።
ኃላፊው አክለውም ተማሪዎቹን ወደ ህክምና ማዕከላት ለመውሰድ አምቡላንሶች ወትምህርት ቤቱ ቅጥር ግቢ ሱገቡ በአከባቢው የተመለከቱ አካላት በፈጠሩት ግርግር ወላጆች ተደናግጠው ወደ ትምህርት ቤቱ መምጣታቸውን ጠቅሰው መንግስት በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ በሁሉም የቅድመ አንደኛ እና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ምገባና ዩኒፎርም ማቅረብን ጨምሮ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ ወላጆችን ከከፍተኛ ወጪ አድኖ በማስተማር ላይ እንደሚገኝ በመግለጽ ወላጆችም በተለያዩ አካላት የሚፈጠሩ አሉባልታዎችን ወደ ጎን በማለት ከመንግስት የሚሰጡ መረጃዎችን መስማት እንደሚጠበቅባቸው አስረድተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምገባ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አንቺነሽ ተስፋዬ በበኩላቸው በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ ትምህርት ቤቶች ወደ 600,000 የሚሆኑ ተማሪዎች የምገባ አገልግሎት በማግኘት ላይ መሆናቸውን ገልጸው ይህንን አገልግሎት 10,000 የተማሪ ወላጅ እናቶች ተደራጅተው መርሀ ግብሩን በኃላፊነት በማከናወን ላይ መሆናቸውን አስገዝበዋል።
ዳይሬክተሯ አክለውም ሀና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የተማሪ ወላጆች በ10 ማህበራት ተደራጅተው የምገባ አገልግሎቱን በመስጠት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው አንዳንድ ሚዲያዎች ጉዳዩ ከሚመለከተው አካል መረጃ ሳይወስዱ ባሰራጩት የተዛባ መረጃ ህብረተሰቡን መረበሻቸውን አስታውቀዋል።
የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ዳክተር ሙልጌታ እንዳለ 714 ተማሪዎች ወደ ህክምና ማዕከላት ሄደው በተደረገላቸው ምርመራ 7 ተማሪዎች ላይ ከታየ የማስመለስ ምልክት በስተቀር በሌሎቹ ላይ ምንም አይነት ከምግብ መመረዝ ጋር የተገናኘ ችግር እንዳላጋጠመ ጠቅሰው የሰባቱ ተማሪዎች የድምና ሰገራ ናሙና ተወስዶ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገ መሆኑንና ውጤቱም እንደታወቀ ለህብረተሰቡ እንደሚገለጽ አስረድተዋል።
መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት ማሰፈንጠሪያዎቹን ይጫኑ!
You Tube: https://www.youtube.com/watch?v=TWkBGoeYCNQ
Telegram ፡ https://t.me/wwwAddisAbabaeducationbureau
Twitter ፡ https://twitter.com/aacaebc
Face book: https://www.facebook.com/aacityeducationcommunication
Blog: – http://www.aacaebc.wordpress.com/
ባልታጠበ እጅ አይንዎን አፍዎን እና አፍንጫዎን ባለመንካት በዙሪያዎ ላሉ ሰዎች አርአያ ይሁኑ!