የኢፌድሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ እና በተመረጡ ትምህርት ቤቶች ባካሄደው የክትትልና ቁጥጥር ተግባር ዙሪያ ውይይት ተካሄደ፡፡
የክትትልና ቁጥጥር ተግባሩ ቦሌ ክፍለ ከተማ በሚገኙ ቦሌ ኮሚኒቲ አንደኛ ደረጃ እና ቦሌ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በሚገኙት ወይራ አምባ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ፤አጃምባ አንደኛ ደረጃ እንዲሁም ጄነራል ዋቆ ጉቱ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተካሄደ ሲሆን የቋሚ ኮሚቴው አባላት በትምህርት ቤቶቹ ያካሄዱትን የመስክ ምልከታ ግብረ መልስ አቅርበው ውይይት ተካሂዱዋል፡፡
የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ ዶክተር ኬይረዲን ተዘራ ቋሚ ኮሚቴው በጠንካራ እና በክፍተት የለያቸውን ጉዳዮች ያቀረቡ ሲሆን በዋናነት ቢሮው በየደረጃው ከሚገኙ የትምህርት መዋቅሮች ጋር ያለው ጠንካራ የስራ ግንኙነት ፤ በአዲስ አበባ የመምህራንን አቅም ለመጎልበትም ሆነ እጥረትን ለመቅረፍ ከአዲስ አበባ እና ከኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲዎች ጋር የተሰሩ ስራዎች፤ በየትምህርት ቤቱ ብቃትን እና የትምህርት ዝግጅትን መሰረት አድርጎ የተካሄደው የርዕሰ መምህራን ምደባ ፤ በትምህርት ቤቶች ለተማሪዎች እየተሰጠ የሚገኘዉን የምገባ አገልግሎትን ጨምሮ ዩኒፎርም እና ሌሎች የመማሪያ ቁሳቁሶች መቅረባቸው እንዲሁም በአብዛኞቹ ትምህርት ቤቶች የተማሪ ክፍል እና የተማሪ መጽሀፍ ጥምርታው በስታንዳርዱ መሰረት መሆኑ በጥንካሬ ከታዩ ተግባራት መካከል እንደሚጠቀሱ አስታውቀዋል፡፡
ምክትል ሰብሳቢው አክለውም በአዲስ አበባ አሁንም ቢሆን ከደረጃ በታች የሆኑ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች መኖራቸው፤ በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች አከባቢ የሚታዩ አዋኪ ነገሮች በችግርነት መቀጠላቸው ፤ በግል ትምህርት ቤቶች አከባቢ ከክፍያ ጋር በተገናኘ የሚነሱ ቅሬታዎች መኖራቸው እንዲሁም የትምህርት ህግ አለመኖሩ በቀጣይ ትኩረት ከሚሹ ተግባራት መካከል በመሆናቸው ሁሉም ባለድርሻ ችግሩን ለመቅረፍ በጋራ መስራት እንደሚጠበቅበት አስገንዝበዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ አድማሱ ደቻሳ በበኩላቸው ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመጡ የሰው ሀብት ልማት ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች የቋሚ ኮሚቴ አባላት በቢሮውም ሆነ በትምህርት ቤቶች የተካሄደው የክትትልና ቁጥጥር ተግባር በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን በመቅረፍ ውጤታማ የመማር ማስተማር ስርዓት ለመፍጠር የጎላ ሚና እንደሚኖረው ጠቁመው ቢሮው በቋሚ ኮሚቴው የተሰጡ ግብረመልሶችን መሰረት በማድረግ የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት አስተባብሮ ውጤታማ ስራ እንደሚሰራ አስረድተዋል፡፡
መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት ማሰፈንጠሪያዎቹን ይጫኑ!
You Tube: https://www.youtube.com/watch?v=TWkBGoeYCNQ
Telegram ፡ https://t.me/wwwAddisAbabaeducationbureau
Twitter ፡ https://twitter.com/aacaebc
Face book: https://www.facebook.com/aacityeducationcommunication
Blog: – http://www.aacaebc.wordpress.com/
Website: – aaceb.gov.et
Email;- aacaebc@gmail.com
Instagram: – https://www.instagram.com/aacaeb/
ባልታጠበ እጅ አይንዎን አፍዎን እና አፍንጫዎን ባለመንካት በዙሪያዎ ላሉ ሰዎች አርአያ ይሁኑ!