የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ት/ቢሮ ባለፉት ዓመታት የትምህርት ሽፋንና ተደራሽነትን በቅድመ መደበኛ ትምህርት
ለማድረስ በርካታ ሥራዎች ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በዚህ ዙሪያ በቅድመ መደበኛ ትምህርት የግል ባለሃብቶች ያበረከቱት አስተዋጽኦ ከአጠቃላይ የዘርፉ እንቅስቃሴ ሲታዩ ድርሻው የላቀ መሆኑ ይታመናል፡፡ በሌላ በኩል በከተማው በሚገኙ የግል ተቋማት ከፍለው መማር የማይችሉ የህብረተሰብ ክፍሎች በቅድመ መደበኛ ትምህርት ተጠቃሚ እንዲሆኑ በመንግስት የመጀመርያ ደረጃ ት/ቤቶች ይህን ፕሮግራም ተግባራዊ ተደርጓል ፡፡ ባለፉት ዓመታት ከፍለው ማስተማር ለማይችሉ የህብረተሰብ ክፍሎች በመንግስት ት/ቤቶች በተዘረጋው የቅድመ መደበኛ ፕሮግራም ተጠቃሚ እንዲሆኑ የተደረገው ጥረት አበረታች ቢሆንም ከአጠቃላይ ተጠቃሚዎች ብዛት አንጻር ሲታይ ግን በቀጣይ ብዙ ሥራ መሥራት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡
በ 2003 ዓ.ም የእቅድ መደበኛ ተቋማት ብዛት 998 የነበረ ሲሆን በ 2007 ዓ.ም 1092 ለማድረስ ተችሏል፡፡ ይኸውም የ8.6% ዕድገት አሳይቷል ፡፡ ይሁን እንጂ በእድገትና ትራንስፎርሜሽን የማጠቃለያ አመት 1200 ተቋማት ይከፈታሉ ተብሎ የታቀደ ቢሆንም የተከፈተው 1092 በመሆኑ አፈፃፀሙ 91% ደርሷል፡፡ በ 2003 ዓ.ም የመንግስት ቅድመ መደበኛ ተቋማት ብዛት 51 ሲሆን በ 2007 ዓ.ም 202 ለማሣደግ ተችሏል፡፡በተጨማሪም ቅድመ መደበኛ መክፈት ባልተቻለባቸው የመንግስት ት/ቤቶች የ “ኦ” ክፍል በመክፈት 6 አመት የሞላቸው ህጻናት አንድ ዓመት ዝግጅት በማድረግ አንደኛ ክፍል እንዲገቡ ለማድረግ የተቻለ ሲሆን የ ኦ ክፍል ተቋማት 66 ሲሆን አጠቃላይ ባለፉት አመታት መንግስት የቅድመ መደበኛ የትምህርት ተደራሽነት ለማሳደግ በሚያስችል መንገድ ለመፈፀም አቅዶ እየሰራ በመሆኑና በተጨማሪም የግል ባለሀብቶች በየዘርፉ ባደረጉት ከፍተኛ ለውጥ ተመዝግቧል፡፡
በ 2003 ዓ.ም የቅድመ መደበኛ አጠቃላይ የተማሪዎች ቁጥር 118840 የነበረ ሲሆን በ 2007 ዓ.ም ወደ 157475 አድጓል ይህም ባለፉት 5 አመታት 24.5 % ዕድገት አሳይቷል ፡፡በሌላ በኩል ከላይ ከቀረበው አጠቃላይ የተማሪዎች ብዛት አኳያ በ 2007 ዓ.ም በመንግስት ቅድመ መደበኛ ተማሪ 35531 (22.55%) ሕጻናት እየተማሩ ይገኛል፡፡
የቅድመ መደበኛ ጥቅልና ንጥር ተሳትፎ
የቅድመ መደበኛ ጥቅል ተሣትፎ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን አመን ዕቅድ 100% ለማድረስ ቢሆንም ማከናወን የተቻለው ግን 92.8% ነው፡፡ የታቀደውን ያህል ማከናወን ያልተቻለበት ምክንያት፣ የአፀደ ሕፃናት መማርያ እድሜ ከ 4-6 ዓመት መሆኑ ቢታወቅም በተግባር ግን ዕድሜያቸው 6 አመት የሆኑ ሕፃናት 1ኛ ክፍል በመግባታቸው መሆኑ ይታወቃል፡፡ንጥር ቅበላ በተመለከተ በ 2003 ዓ.ም 68% የነበረ ሲሆን በ 2007 ዓ.ም 79.64% ማድረስ ተችሏል ፡፡ ይኸውም በ 2007 ዓ.ም በቅድመ መደበኛ ተማሪዎች በመማሪያ ዕድሜያቸው (ከ4-6 ዓመት) ካለፉት ዓመታት በተሻለ ሁኔታ በመማር ላይ መሆናቸውን ያሳያል፡፡ ነገር ግን ንጥር ተሳትፎ 100% ማድረስ ያልተቻለው ሕፃናት ከ3 ዓመት ጀምሮ ት/ቤት እየገቡ መሆናቸው ታውቋል፡፡